July 31, 2019

የኮሌራ ወረርሽኝ አዲስ አበባን ጨምሮ በተለያዩ ክልሎች መከሰቱን ኢንስቲዩቱ አስታወቀ


የኮሌራ ወረርሽኝ አዲስ አበባን ጨምሮ በትግራይ፣ በኦሮሚያ፣ ሶማሌና አማራ ክልሎች በተለያዩ አካባቢዎች መከሰቱን የኢትዮዽያ ህብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት አስታወቀ::

በአዲስ አበባ ከተማ በአቃቂ እና አዲስ ከተማ ክፍለ ከተሞች በአጣዳፊ ተቅማጥ እና ትውከት ህመም ህክምና እያገኙ ካሉ 5 ሰዎች ውስጥ አንዱ በላብራቶሪ ቪብሮ ኮሌራ መሆኑ የተረጋገጠ ሲሆን ለሁሉም ህክምና እየተሰጠ እንደሚገኝ ኢንስቲትዩቱ ገልጿል::

በተመሳሳይ መልኩ የአጣዳፊ ተቅማጥና ትውከት ህመም በኦሮሚያ፣ አማራ፣ ትግራይና ሶማሌ ክልሎች በአጠቃላይ በ360 ሰዎች ላይ የታየ ሲሆን ከእነዚህም ውስጥ 8 የሚሆኑት በላብራቶሪ የኮሌራ በሽታ መሆኑ ተረጋግጧል ብሏል::
እንደ ኢቢሲ ዘገባ ሁሉም አስፈላጊውን ህክምና እያገኙ ሲሆን በቅርቡ ለበሽታው

በከፍተኛ ሁኔታ ተጋላጭ ለሆኑ የህብረተሰብ ክፍሎች የክትባት አገልግሎት ለመስጠት ዝግጅት መጠናቀቁን ኢንስቲትዩቱ
አብራርቷል::

ሁሉም የህብረተሰብ ክፍል ይህንን በመገንዘብ አስፈላጊውን ሁሉ ጥንቃቄ ማድረግና ምልክቱ የታየባቸው ሰዎች በፍጥነት ወደ ጤና ተቋማት በመሄድ ህክምና ማግኘት ይኖርባቸዋል ተብሏል::

በበሽታው የተያዘ ሰው በተደጋጋሚ አጣዳፊ ተቅማጥና ትውከት ይኖረዋል፡፡ በዚህም የተነሳ የሰውነት ፈሳሽና ጠቃሚ የሆኑትን ንጥረ ነገሮች መጠን ያዛባል፡፡

በተጨማሪም
• አጣዳፊ መጠነ ብዙ የሆነ ውኃማ ተቅማጥ
• ትውከትና ቁርጥማት
• የአይን መሰርጐድ
• የአፍና የምላስ መድረቅ
• እንባ አልባ መሆን
• የሽንት መጠን መቀነስ
• የቆዳ ድርቀትና መሸብሸብ በመጨረሻም ከፍተኛ የሆነ የሰውነት ድርቀት በማስከተል ህመምተኛው በወቅቱ ካልታከመ ለሞት ሊያበቃው ይችላል፡፡

መከላከያና መቆጣጠሪያ መንገዶች

• መፀዳጃ ቤት መገንባትና በአግባቡ መጠቀም
• ምግብን በሚገባ አብስሎ መመገብ
• በውኃ /መድኃኒት/ በውኃ አጋር/ የታከመ ውሃ ለመጠጥ መጠቀም ወይም ውኃ አፍልቶና አቀዝቅዞ መጠጣት
• እጅን በውኃና በሳሙና /በአመድ በደንብ አጥርቶ መታጠብ
• ከመፀዳጃ ቤት መልስ መታጠብ
• ምግብ ከማዘጋጀትዎ በፊት መታጠብ
• ምግብ ከመመገቦ በፊትና በኋላ በደንብ መታጠብ
• ህጻናትን ካፀዳዱ በኋላ መታጠብ
ማንኛውም ከቤት የሚወጣ ደረቅ ወይም ፈሳሽ ቆሻሻ አካባቢን ወይንም ውኃን እንዳይበክል በአግባቡ ማስወገድ፡፡ ምልክቱ የታየበት ህመምተኛ ፈጥኖ ወደ ህክምና ተቋም በመሄድ ሊታከም ይገባል፡፡